የትግላችን ግብ ሕዝቡን የሥልጣን ባለቤት ማድረግ ነው!
ዓለም አቀፉ የሣናባ ቆልፍ (ኮቪድ-19) የተሰኘው ተላላፊ በሽታ በጋረጠው ችግር ሳቢያ፣ ላለፉት 28 ዓመታት፣ ያልተመረጡትን ተመረጡ እያለ «ሲያስመርጥ» የነበረው «የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ» 6ኛውን ዙር ብሔራዊና ክልላዊ ምርጫ ወቅቱን ጠብቆ ማካሄድ እንዳይቻል እንዳደረገው አሳውቋል። እንደዚህ ያሉ ያልተጠበቁ ሁኔታዎች ሲከሰቱ በምን መንገድ ችግሮቹን መወጣት እንደሚቻል፣ ሕገ-መንግሥቱ የደነገገው ባለመኖሩ፣ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች የተለያዩ የመፍትሔ ሀሳቦችን ሲሰነዝሩ እያስተዋልን ነው። በርካታዎቹ ከመጀመሪያውም ሕዝቡ የታገለው እና እየታገለም ያለው የአገሪቱና የሕዝቡ የችግር ቋጠሮው ሕገ-መንግሥቱ ስለሆነ፤ እርሱ መለወጥና በአዲስ ሕዝቡ የኔ በሚለውና የሕዝቡን ፍላጎት ያካተተ ሕገ-መንግሥት ይተካ። ለዚህም የሽግግር ሥርዓት ይኑረን የሚለው የብዙዎቹ ድርጅቶች ጥያቄ መሆኑ ይታወሳል። የዚህ ሀሳብ አራማጆች አክለውም በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ለሽግግር መንግሥት ምሥረታ ፈቃደኛ ካልሆነ ደግሞ፣ የምርጫ ጊዜው መራዘም አለበት፣ የሚል አቋም ይዘው በኅብረትም በተናጠልም ሲያሰሙ መቆየታቸው አይዘነጋም።